የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ሕግ በማስከበር ሂደት ላይ ጉዳት ለደረሰባቸውና ደም ለሚያስፈልጋቸው የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ የአማራ ክልል ልዩ ኃይልና ሚሊሻ አባላት አጋርነታቸውን ለመግለጽ ኅዳር 14/2013 ዓ.ም በሁሉም ካምፓሶች ደም የመለገስ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡

በዩኒቨርሲቲው የሕክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር ወ/ሮ ወይንሸት ገ/ፃዲቅ እንደተናገሩት የደም ልገሳው ዋና ዓላማ ለሀገር ሰላምና ደኅንነት መስዋዕትነት እየከፈለ ለሚገኘው የሀገር መከላከያ ሠራዊት የበኩላችንን አስተዋፅኦ ማበርከት ነው፡፡ ፎቶዎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ

በኮሌጁ የሄማቶሎጂ መ/ር አቶ አስቻለው መስፍን ሕግ በማስከበር ላይ ለሚገኘው ሠራዊት የምሰጠው ደም ትንሹ ሰጦታዬ ነው፤ በዚህም በጣም ደስተኛ ነኝ ብለዋል፡፡

የ4ኛ ዓመት ነርሲንግ ተማሪ የሆነችው ሃና መስፍን በበኩሏ በአሁኑ ሰዓት ሠራዊቱን መደገፍ የምትችለው በሞራልና ደም በመለገስ መሆኑን ገልጻ ይህንንም በማድረጓ ሀገራዊና ወገናዊ ስሜት የሚሰማት መሆኑን ተናግራለች፡፡

በደም ልገሳ ፕሮግራሙ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንትን ጨምሮ ም/ፕሬዝደንቶች፣ የኮሌጅና የት/ቤቶች ዲኖች፣ መምህራን፣ ተማሪዎችና የአስተዳደር ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞች ተሳትፈዋል፡፡ በእስካሁኑ ሂደትም ከነጭ ሳር ካምፓስ 30፣ ከጫሞ ካምፓስ 28፣ ከዋናው ግቢ 27፣ ከዓባያ ካምፓስ 12 እና ከኩልፎ ካምፓስ 6 ዩኒት በድምሩ 103 ዩኒት ደም ተሰብስቧል፡፡

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት