የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሕክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ከኢትዮጵያ ሕክምና ማኅበር ጋር በመተባበር ‹‹ጠንካራ እና ታማኝ ሐኪም ለተሻለ ጤና!›› በሚል መሪ ቃል በኮሌጁ ሥር ለሚገኙ የሕክምና ባለሙያዎች ታኅሣሥ 17/2013 ዓ/ም በሙያ ማሻሻያ ዙሪያ ሥልጠና የሰጠ ሲሆን የጋራ መግባቢያ ሰነድም ተፈራርሟል፡፡   ፎቶዎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ


የሕክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ቺፍ ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ዶ/ር ታምሩ ሽብሩ ከዚህ ቀደም ኮሌጁ ከኢትዮጵያ ሕክምና ማኅበር ጋር በመተባበር ከተለያዩ አካባቢዎች የሕክምና ባለሙያዎችን በመጥራት በሙያ ማሻሻያ ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና እንደሰጠ ገልጸዋል፡፡ የማኅበሩን እንቅስቃሴ ለመደገፍ የቢሮ እና የቁሳቁስ ድጋፍ ማድረጉንም ዶ/ር ታምሩ  ተናግረው ጥራት ያለው ሕክምና ለማኅበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ የሕክምና ባለሙያዎች የማኅበሩ አባል በመሆን የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሕክምና ማኅበር አርባ ምንጭ ቅርንጫፍ ፕሬዝደንት ዶ/ር ታዲዮስ ኃይሉ ማኅበሩ ለሕክምና ባለሙያዎች በምርምር፣ በሙያ ማሻሻያ፣ አጫጭር የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ ምቹ የሥራ አካባቢ በመፍጠር፣ የማኅበሩ አባላትን በማነቃቃትና በማሳተፍ እንዲሁም ከሕክምና ሙያ ፈቃድ ጋር ተያይዘው ለሚነሱ ጉዳዮች ተገቢ ምላሽ  በመስጠት ረገድ በርካታ ሥራዎች እየሠራ ይገኛል ብለዋል፡፡
የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት