Print

የስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ዳይሬክቶሬት ለተማሪዎች መኝታ አገልግሎት ተቆጣጣሪዎች በስነ-ምግባር ደንብና በሙስና ወንጀል ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና የካቲት 16/2015 ዓ/ም ሰጥቷል፡፡ ተጨማሪ ፎቶዎችን ለማየት እዚህ ይጫኑ፡፡

የዳይሬክቶሬቱ ዳይሬክተር ወ/ሮ እታፈራሁ መኮንን ሥልጠናው ሠራተኞች የሚጠበቅባቸውን ስነ-ምግባራዊ ባህርያትና እሴቶች በመላበስ ሙስናና ብልሹ አሠራርን የሚፀየፉ እንዲሆኑ ማስቻልና በዕውቀት፣ በክሂሎትና በአስተሳሰብ የተሻለ ሠራተኛ ለተቋሙ ለመፍጠር የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የዳይሬክቶሬቱ ባለሙያና አሠልጣኝ አቶ እንዳለ ኢልቶ የሥልጠናው ዓላማ የስነ-ምግባርና የሙስና ጽንሰ ሃሳቦችን ለሠራተኞች ግንዛቤ ማስጨበጥና ራሳቸውን ከሙስና ጠብቀው በተቋሙ መልካም አፈፃፀም ላይ ባለድርሻ አካል እንዲሆኑ ማብቃት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሌላኛው የዳይሬክቶሬቱ ባለሙያና አሠልጣኝ አቶ ተመስገን ታደሰ በበኩላቸው የተማሪዎች መኝታ አገልግሎት ተቆጣጣሪዎች ሥራቸው በስፋት ከተማሪዎች ጋር የሚገናኝ በመሆኑ ሥልጠናው በመልካም ሥነ-ምግባር አገልግሎት የሚሰጡበትን መንገድ የሚያሳይና ራሳቸውን እንዲያዩ፣ ተነሳሽነት እንዲኖራቸውና መመሪያዎችን በተግባር እንዲፈፅሙ የሚያደርግ ነው ብለዋል፡፡

ሠልጣኞች በሥልጠናው የመልካም ስነ-ምግባር አስፈላጊነትን መገንዘባቸውን ተናግረው የመኝታ አገልግሎት ተቆጣጣሪ ሠራተኞች የተሰጣቸውን ኃላፊነት በታማኝነት፣ በቅንነትና በውጤታማነት ለመፈፀም የስነ-ምግባር መርሆችን ተግባራዊ ማድረግ እንዳለባቸው አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

የብሩህ ተስፋ ማዕከል!

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት