የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ትኩረት የሚሹ የቆላማ አካባቢ በሽታዎች ምርምርና ሥልጠና ማዕከል በደቡብ ኦሞ ዞን በተለይም በሙርሲ አካባቢ የቪሰራል ሌሽማኒያሲስ/Visceral Leishmaniasis/ በሽታ ተጠቂዎች ቁጥር ማሻቀብን ተከትሎ የምርመራ ናሙና ለሚወስዱ ሐኪሞችና ወረርሽን መከሰት አለመከሰቱን ለማረጋገጥ ዳሰሳ ለሚያካሂዱ ከዞኑ ወረዳዎችና ከጂንካ ከተማ ለተወጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎች የካቲት 25/2015 ዓ/ም ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ ፎቶዎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ

ትኩረት ከሚሹ የቆላማ አካባቢ በሽታዎች አንዱ የሆነው የውስጥ አካል ሌሽማኒያሲስ ሌሽማኒያ በሚባል ጥገኛ ተሕዋስ ዝርያ የሚመጣ በሽታ ሲሆን የአሸዋ ዝንብ (Sand fly) በተባለች ትንኝ ንክሻ አማካኝነት የሚተላለፍና በአግባቡ ካልታከሙት ጉበትን፣ ጣፊያንና ሌሎች የውስጥ አካላትን በመጉዳት እስከ ሞት የሚያደርስ ነው፡፡ በደቡብ ኦሞ ዞን የተለያዩ አካባቢዎች የበሽታው ተጠቂዎች ቁጥር በመጨመሩ ዞኑ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲን ድጋፍ በመጠየቁ ዳሰሳ ለሚያካሂዱ ባለሙያዎች በጂንካ ከተማ ሥልጠናው የተሰጠ ሲሆን ከዚህም ጎን ለጎን የጂንካ ሆስፒታል ሐኪሞች በሽታውን በላቦራቶሪ ለመለየት ከጣፊያ ናሙና አወሳሰድ ላይ በዩኒቨርሲቲው ስፔሺያሊስት ሐኪም ተግባራዊ ሥልጠና ወስደዋል፡፡

ትኩረት የሚሹ የቆላማ አካባቢ በሽታዎች ምርምርና ሥልጠና ማዕከል ዳይሬክተር ረ/ፕ ጸጋዬ ዮሐንስ በአሁኑ ሰዓት በደቡብ ክልል የተለያዩ ቦታዎች የቆላማ አካባቢ በሽታዎች መከሰታቸውን ጠቁመው በጋሞ ዞን ቁጫ አካባቢ ‹‹የሰው የአፍሪካ ትሪፓናሶሚያሲስ/Human African Trypanosomiasis››፣ በጋሞ ዞን ቦረዳና ዲታ ወረዳዎች ‹‹ቦልቦ/Cutaneous Leishmaniasis›› እና በደቡብ ኦሞ ዞን ‹‹ቪሰራል ሌሽማኒያሲስ/Visceral Leishmaniasis››ን አስመልክቶ ማእከሉ በግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎች፣ ምርምሮች፣ በሕክምና ግብአቶችና በሌሎችም ድጋፎች የበኩሉን እየተወጣ ነው ብለዋል፡፡

በደቡብ ኦሞ ዞን ቪሰራል ሌሽማኒያሲስ መከሰቱን ተከትሎ ዞኑ ባቀረበው ጥያቄ መነሻነት ቀደም ሲል ከኮሌጁ የተውጣጡ ባለሙያዎች ቡድን ከዞኑ ጤና መምሪያ፣ ከጂንካ ሆስፒታልና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ውይይት መሠረት ዩኒቨርሲቲው ከጤና ሚኒስቴርና ከዓለም የጤና ድርጅት ጋር በመተባበር የክሊኒካልና ላቦራቶሪ የንድፈሃሳብ ሥልጠና በአርባ ምንጭ ከተማ መስጠቱን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡ ቀጣይ የተግባር ሥልጠናና ወረርሽኝ መከሰቱን ለማረጋገጥ የዞኑ ጤና መምሪያ ለሚያዋቅረው ቡድን የወረርሽኝ ዳሰሳ ሥልጠናዎቹን በጂንካ ከተማ ማዘጋጀቱን እንዲሁም ሥራውን በዕውቀት፣ በክሂሎት፣ በገንዘብና በግብአት ለመደገፍ ማእከሉ ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የጂንካ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር ተስፋኢየሱስ ተፈራ ቀደም ሲል በሆስፒታሉ አልፎ አልፎ ለሚመጡ የሌሽማኒያሲስ ታካሚዎች ሕክምና ሲሰጥ እንደነበር አስታውሰው በ2015 ዓ/ም በተለይም ባለፉት ሁለት ወራት የታካሚዎች ቁጥር ከወትሮው በላቀ ሁኔታ መጨመሩን ተናግረዋል፡፡ የታካሚዎች ቁጥር በድንገት ማሻቀብ፣ የሆስፒታሉ የቅበላ አቅም ማነስ፣ የደም እጥረት፣ ለበሽታው የሚሆኑ መመርመሪያዎችና መድኃኒቶች አለመኖር፣ የባለሙያ እጥረት እንዲሁም በሽታው የሰውነትን የመከላከል አቅም የሚያዳክምና ታካሚዎች ለሌሎች በሽታዎች ተጋላጭ በመሆናቸው የተጨማሪ መድኃኒቶችና አጋዥ ፈሳሾች እጥረት ሕክምናውን በአግባቡ ለመስጠት አዳጋች እንዳደረገው ዶ/ር ተስፋኢየሱስ ገልጸዋል፡፡

እንደ ሜዲካል ዳይሬክተሩ በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ሆነው አስከ አሁን 130 ታካሚዎችን ያስተናገዱ ሲሆን ‹‹ሜዲሲንስ ሳንስ ፍሮንታየርስ ቤልጂዬምMédecins Sans Frontières (MSF) Belgium›› ከተሰኘ የሕክምና ሰብአዊ ድጋፍ ግብረ ሠናይ ድርጅት ድጋፎች ማግኘት ጀምረዋል፡፡ የምርመራ ሂደቱን አስመልከቶ ከዚህ ቀደም አርኬ 39/rK39/ የመመርመሪያ ኪት ይጠቀሙ እንደነበር ገልጸው መመርመሪያው እንደ መጀመሪያ ደረጃ መለያ የሚያገለግልና የተሳሳቱ ውጤቶችን የማሳየት ዕድሉ ሰፊ በመሆኑ ታካሚዎችን ወደ ኮንሶና አርባ ምንጭ እንልክ ነበር ብለዋል፡፡ በሽታውን በትክክል ለመለየት ከጣፊያ ናሙና በመውሰድ የሚሠራው የምርመራ ዘዴ (Splenic Aspiration) ላይ ዩኒቨርሲቲው ለሆስፒታሉ ሐኪሞች የተግባር ሥልጠና በመስጠቱ በቀጣይ ለታካሚዎቻቸው ተገቢውን ምርመራ እንደሚያደርጉና ከሕክምናው በኋላ ላለው ክትትል እንደሚረዳቸውም ተናግረዋል፡፡

ተግባራዊ ሥልጠናውን የሰጡት በሕክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ መምህርና በአርባ ምንጭ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ስፔሺያሊስት ዶ/ር አክሊሉ ሙሐመድ እንደገለጹት ቪሰራል ሌሽማኒያሲስ አብዛኛው ምልክቶቹ ከወባ በሽታ ምልክቶች ጋር ተመሳሳይነት ስላላቸው ወባ ተብሎ የመታከም ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ በርካታ ታካሚዎች የወባ መድኃኒት ሲወስዱ ቆይተው ባለመዳናቸው ለተጨማሪ ሕክምና ሲመጡ ሌሺማኒያሲስ ሆኖ ይገኛል ያሉት ዶ/ር አክሊሉ በአንጻሩ ሕመሙ መኖሩ በትክክል ሳይረጋገጥ መድኃኒት መስጠቱ የጎንዮሽ ጉዳት የሚያስከትል ከመሆኑም ባሻገር መድኃኒቱ በቀላሉ የማይገኝ እንደመሆኑ የመድኃኒት እጥረት የሚያስከትልም ነው ብለዋል፡፡

እንደ ዶ/ር አክሊሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ በተቀመጠው መስፈርት መሠረት የበሽታው አምጪ ተሕዋስ መኖሩ ከጣፊያ በሚወሰድ ናሙና በቀጥታ ተረጋግጦ መታከም ያለበት ሲሆን ሕክምናው ከተሰጠ በኋላ መዳኑን ለማረጋገጥ በድጋሚ ናሙና መወሰድ ይኖርበታል፡፡ በተግባር ሥልጠናው በናሙና መውሰድ ሂደት የደም መፍሰስን እንዲቆም የሚያደርገው ፕላትሌት መጠን መለካት፣ በቂ መጠባበቂያ ደም መኖሩን ማረጋገጥና የመሳሰሉ ቅድመ ጥንቃቄዎች እንዲሁም ናሙና ከተወሰደ በኋላ ታካሚው ቢያንስ ለ8 ሰዓታት እንቅስቃሴ ሳያደርግ የቅርብ ክትትል ማድረግና ሌሎችም ሊከሰቱ የሚችሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ላይ ግንዛቤ በማስጨበጥ የሆስፒታሉ ሁለት ሐኪሞች ከታካሚዎች ናሙና እንዲወስዱ ተደርጓል፡፡ ሐኪሞቹ ናሙና መውሰድ መጀመራቸው ከምርመራ ሂደት ጋር የተያያዙ ችግሮችን የሚቀርፍ መሆኑን ዶ/ር አክሊሉ ተናግረዋል፡፡

የወረርሽኝ ዳሰሳ ሥልጠናውን የሰጡት በሕክምናና ጤና ሣይንስ ኮሌጅ የኅብረተሰብ ጤና ት/ቤት መምህር አቶ መስፍን ቆቴ እንደገለጹት ሥልጠናው የደቡብ ኦሞ ዞን ትኩረት የሚሹ የቆላማ አካባቢ በሽታዎች ተጠሪዎች እና ለዚሁ ሥራ የተቀጠሩ የክትትል ባለሙያዎችን ያካተተ ሲሆን የዳሰሳው አስፈላጊነት፣ የሚከናወንበት ጊዜ፣ ከማረጋገጫው በኋላ የሪፖርት አዘገጃጀት ርዕሰ ጉዳዮችን ዳስሷል፡፡

እንደ አሠልጣኙ ሌሽማኒያሲስን አስመልክቶ የጤና ሚኒስቴር ዝቅተኛ የተጠቂ መጠን/Threshold Limit/ ያላስቀመጠ በመሆኑ ወረርሽን መሆን አለመሆኑን ለመለየት የቀደሙ ዓመታት መረጃዎች በማገናዘብ የበሽታውን አሁናዊ ስርጭትና የክስተት መጠን ሲወዳደር ባልተለመደ መልኩ በጣም ጨምሮ ከተገኘ ወረርሽኝ ተከስቷል ልንል እንችላለን፡፡

የደቡብ ኦሞ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ አብርሃም አታ በዞኑ ለተከሰተው ችግር ዩኒቨርሲቲው የበኩሉን ኃላፊነት ለመወጣት ስላደረገው ጥረት ምስጋና አቅርበው በቀጣይ ለዳሰሳው የሚዋቀረውን ቡድን ለመደገፍም ሆነ ሌሎች ሙያዊ አስተዋጽኦዎችን ለማበርከት ከጎናቸው እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

የብሩህ ተስፋ ማዕከል!

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት