ወ/ሮ መርታን መርዕድ ከአባታቸው ከአቶ መርዕድ ዱለቻ እና ከእናታቸው ወ/ሮ አየለች ቡሩኮ በአርባ ምንጭ ከተማ ወዜ ቀበሌ ጳጉሜ 3/1978 ዓ.ም ተወለዱ፡፡
የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን (ከ1ኛ - 6ኛ) ክፍል በዓለም 1ኛ ደረጃ ት/ቤት፣ የ7ኛ እና 8ኛ ክፍል ትምህርታቸውን በኩራዝ መለስተኛ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት እንዲሁም የ2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በጂንካ አጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ያጠናቀቁ ሲሆን በ1996 ዓ.ም ሚዛን ቴፒ ግብርና ኮሌጅ በመግባት በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ትምህርት በ1998 ዓ/ም በዲፕሎማ ተመርቀዋል፡፡
ወ/ሮ ማርታን ከነሐሴ 1998 እስከ 2000 ዓ/ም በቀበሌ ልማት ጣቢያ በተፈጥሮ ሀብት ባለሙያነት እንዲሁም ከ2000 - 2003 ዓ/ም በዳሰነች ወረዳ አርብቶ አደር ልማት ጽ/ቤት በባለሙያነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡
ወ/ሮ መርታን በ2003 ዓ/ም በወረዳው ባገኙት የክረምት ትምህርት ዕድል ወደ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በመግባት በ2007 ዓ.ም በተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃ ዘርፍ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያገኙ ሲሆን በ2013 ዓ/ም እንዲሁ የ2ኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን ለመከታተል በዳሰነች ወረዳ ስፖንሰርነት ባገኙት ዕድል በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ጂኦግራፊ ትምህርት ክፍል በ‹‹Environment and Sustainable Development›› የትምህርት መስክ ትምህርታቸውን ለማጠናቀቅ የመመረቂያ ጽሑፋቸውን ለምዘና ለማቅረብ ዝግጅት እያደረጉ ነበር፡፡
ወ/ሮ መርታን መርዕድ ባለትዳርና የ1 ወንድ እና የ2 ሴት ልጆች እናት ሲሆኑ ባደረባቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መስከረም 8/2015 ዓ.ም በተወለዱ በ37 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በወ/ሮ መርታን መርዕድ ኅልፈት የተሰማውን ሐዘን እየገለፀ ለሟች ቤተሰቦች፣ ወዳጅ ዘመዶች፣ ጓደኞችና የሥራ ባልደረቦች መጽናናትን ይመኛል፡፡
የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት